በኢንቨስትመንት አዋጭነት ጥናት ላይ ያነጣጠረው ተቋም

የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ከመነቃቃት አልፎ፣ ዕድገት እያስመዘገበ መሆኑን መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ የአገሪቱ ኢኮኖሚ በተለያየ መስክ ዕድገት እየተመዘገበበት ይገኛል፡፡ ከእነዚህም መስኮች አንዱ የወጭ ንግድ ዘርፍ ነው፡፡
ምንጭ፥ ሪፖርተር ጋዜጣ
የወጭ ንግድ ዘርፍ በየዓመቱ ዕድገት እያስመዘገበ ቢሆንም አገሪቱ ካላት እምቅ ሀብት አንፃር ዕድገቱ ብዙም የሚጠበቀውን ያህል አልሆነም፡፡ የወጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት ዕድገት ቢያሳይም የሚጠበቀውን ያህል ግን አይደለም፡፡ የወጭ ንግድ ዘርፍን በዋነኛነት የተሸከመው የግሉ ዘርፍ ሲሆን፣ ዘርፉ ከተፈጠረ ከሁለት አሠርታት የዘለለ ባለመሆኑ ድጋፍ እንደሚያስፈልገው አይካድም፡፡
በተለይ የወጭ ንግድ ምርቶችን መዳረሻዎችን ከማስፋት በተጨማሪ የውጪ ዓለም ስለኢትዮጵያና ስለኢትዮጵያ ምርቶች ግንዛቤ እንዲያገኝ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ በዋነኝነት ይህንን ክፍተት ለመድፈን፣ ብሎም የአገር ውስጥ ምርቶች ብራንድ (መለያ) እንዲኖራቸው፣ ብራንዳቸውም ተለይቶ እንዲታወቅ ለማድረግና ፋይዳ ያላቸውን ዝግጅቶች ለማዘጋጀት ዋፋ ማርኬቲንግና ፕሮሞሽን ድርጅት ተቋቁሟል፡፡ ኩባንያው ከተመሠረተ ጀምሮ ያከናወናቸው ሥራዎችንና በቀጣይነት ስለሚያካሒዳቸው ተግባራት ውድነህ ዘነበ የዋፋ ማርኬቲንግና ፕሮሞሽን ኩባንያ ዋና ሥራ አስኪያጅ ወይዘሮ ፋንታዬ ጌታነህን አነጋግሯቸዋል፡፡
ሪፖርተር፡- ዋፋ ማርኬቲንግና ፕሮሞችን መቼና ለምን ተቋቋመ?
ወ/ሮ ፋንታዬ፡- ዋፋ ማርኬቲንግና ፕሮሞሽን ኩባንያ በ2001 ዓ.ም. ነው የተቋቋመው፡፡ ኩባንያው በዋናነት ሦስት ነገሮችን ይዞ ነው የተቋቋመው፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ ዓለም አቀፍና አገር አቀፍ ዝግጅቶች ማዘጋጀት፣ በማስታወቂያ ደረጃ ደግሞ ብራንዲንግ ማድረግ በሌላ በኩል በሲኒማውም ዘርፍ በተወሰነ ደረጃ የመግባት ፍላጎት አለን፡፡ በዋነኛነት ግን ዓለም አቀፍና አገር አቀፍ ዝግጅቶችን ማዘጋጀት ላይ እናተኩራለን፡፡
ሪፖርተር፡- ዓለም አቀፍ ዝግጅቶችን ሲባል ምን ዓይነት ሥራዎችን ያካትታል?
ወ/ሮ ፋንታዬ፡- አገራችን የውጭ ባለሀብቶችን የመሳብ ፍላጎት አላት፡፡ እስካሁን ባሉት ጊዜያት በቂ የሚባል ባለሀብት ወደ አገር ውስጥ አልገባም፡፡ የውጭ ባለሀብቶችም በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሥራ ውስጥ በሰፊው እንዲገቡ የምንሠራው ሥራ አለ፡፡ ሁለተኛው ቱሪዝም ላይ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ከበርካታ አገሮች ጋር ስትነፃፀር የተሻለ የቱሪዝም መስህብ ቢኖራትም፣ ከዘርፉ የምታገኘው ገቢ ደግሞ አነስተኛ ነው፡፡ ስለዚህ በቱሪዝም ዘርፍ የአገራችንን መልካም ገፅታ እንገነባለን፡፡ ኢትዮጵያ ረዥም ዓመት በድርቅና ረሀብ ትታወቃለች፡፡ ይህንን በመፋቅ አገራችን ያሏትን ሀብቶች በማስተዋወቅ የውጭ ቀጥተኛ መዋለ ንዋይ ፍሰቱ እንዲጨምር እንሠራለን፡፡ እስካሁን አሜሪካ ሁለት ጊዜ ዓለም አቀፍ ኢቨንት (ሁነት) አዘጋጅተናል፡፡ እንግሊዝ፣ ጣልያን፣ ሕንድ፣ ሩስያ በቅርቡ ደግሞ ጃፓንና ደቡብ ኮርያ ዝግጅት እናካሒዳለን፡፡
ሪፖርተር፡- ከዚህ ሥራችሁ ምን ውጤት ተገኘ?
ወ/ሮ ፋንታዬ፡- እስካሁን ድረስ በእነዚህ አገሮች ውስጥ ባካሄድናቸው የተለያዩ ዝግጅቶች ከሁለት ሺሕ በላይ ባለሀብቶች አግኝተናል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ አብዛኞቹ ወደ አገር ውስጥ መጥተዋል፡፡ ባለሀብቶች የመጡት አንድም ኢንቨስት ለማድረግ፣ ሁለትም ለመጎብኘት ነው፡፡ ይሄ ለአገራችን የሚሰጠው ጠቀሜታ ቀላል አይደለም፡፡ እንገፋበታለን፡፡
ሪፖርተር፡- ምን ዓይነት ምርቶችን ነው በውጭ አገር የምታስተዋውቁት?
ወ/ሮ ፋንታዬ፡- አንድ የኢንቨስትመንት ፎረም ለማዘጋጀት ከአራት እስከ ስድስት ወር ይፈጅብናል፡፡ ይህ ፎረም ምንድነው የሚያካትተው? በመጀመርያ በፎረሞቹ ላይ 70 በመቶ የሚሆነውን የግሉ ዘርፍ እናሳትፋለን፡፡ ለምሳሌ ፎረሙ የሚካሄደው ሩስያ፣ ሞስኮ ከሆነ የሞስኮ ፍላጎት ምንድነው? የሚለውን እናጠናለን፡፡ የግብርና ምርት ነው ወይ? ማዕድን ነው ወይ? ማኑፋክቸሪንግ ነው ወይ? የሚለውን እናጠናለን፡፡ በጥናታችን መሠረት የተሠማሩ የግሉ ዘርፍ ተዋናዮችን እናሳትፋለን፡፡ በዚህም ከፍተኛ ውጤት ታይቷል፡፡ ለምሳሌ በሞስኮ የደራ የአበባ ገበያ አለ፡፡
የኢትዮጵያ አበባ ሞስኮ የሚሸጠው ከሌላው አገር ገበያ ነው፡፡ ሞስኮ ላይ ፕሮግራም ካዘጋጀን በኋላ በዚህ ሳምንት መጀመርያ የሞስኮ ባለሀብት በቀጥታ የኢትዮጵያን አበባ ከኢትዮጵያ ለመውሰድ የሚያስችለውን ስምምነት ለማድረግ አዲስ አበባ መጥቷል፡፡ ባለሀብቱ ከአበባ ዘርፍ ተዋናዮች ከንግድ ሚኒስቴርና ከኢትዮጵያ አየር መንገድ ጋር ድርድሩን አካሂዷል፡፡ ይህ ማለት በሚቀጥሉት ጊዜያት የኢትዮጵያ አበባ በቀጥታ ሞስኮ ይሄዳል ማለት ነው፡፡
ሪፖርተር፡- በውጭ አገር የዚህ ዓይነት ዝግጀቶች ከተካሄዱ በኋላ የሚመጡ ኢንቨስተሮችን በማስተናገድ በኩል አለመናበብ እንዳለ ይነገራል፡፡ እናንተ ይህንን ችግር አስተውላችሁታል?
ወ/ሮ ፋንታዬ፡- አንዱና ትልቁ ችግር የሆነው እኛ ኢንቨስትመንት ፎረሙን አካሂደን እንመጣለን፡፡ ከመጣን በኋላ ኢንቨስተሮቹ ወደ ኢትዮጵያ ይመጣሉ፡፡ ኢትዮጵያ ከመጡ በኋላ ማነው የሚያገኛቸው? የሚያገኛቸው ደላላ ነው፡፡ አንዳንድ ቦታ እንዲሁም ባለሀብቶቹ ኢንቨስት ሲያደርጉ 30 በመቶ ድርሻ ለደላላው መስጠት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ብዙ ዓይነት መዘበራረቅ አለ፡፡ ሁለተኛ ደግሞ ኢንቨስተሮቹ ከፎረሙ በኋላ ወዲያውኑ ቢመጡ ምንድነው የምንሰጣቸው፡፡ የተጨበጠ ፕሮጀክት አለን ወይ? ፕራይቬታይዜሽን ኤጀንሲ የትኞቹ የልማት ድርጅቶች ነው የሚሸጠው? በስንት ብር? የሚሉት ነጥቦች አልተመለሱም ነበር፡፡ እኛ ኢንቨስትመንት ፎረሙን አካሂደን እንመጣለን፡፡
ኢንቨስተሮቹ ይመጣሉ፡፡ አንዴ ውጭ ጉዳይ፣ አንዴ ኢንቨስትመንት ኤጀንሲ፣ አንዴ ንግድ ሚኒስቴር ይሄዳሉ፡፡ አንዳንዶቹ ተንከራተው ተስፋ ቆርጠው ወደ አገራቸው ይመለሳሉ፡፡ አንዳንዶቹ ተሳክቶላቸው ይሠራሉ፡፡ መናበብ ያስፈልጋል፡፡ እኛ እየሞከርን ያለነው ኢንቨስትመንት ፎረሙን ካካሄድን በኋላ የሚመጡ ባለሀብቶች እኛ ጋ በቀጥታ እንዲመጡ፣ ከዚያ በኋላ የማስተባበሩን ሥራ እንድንሠራ ነው፡፡ ከዚያ በኋላ የአዋጭነት ጥናት እንሠራላቸዋለን፡፡ ኢንቨስትመንት ፈቃድ እናወጣላቸዋለን፡፡ የሚያስፈልጓቸውን ሥራዎች በተቀላጠፈ መንገድ እናከናውንላቸዋለን፡፡ እያንዳንዱ ጠብታ ገንዘብ ለመንግሥት ይገባል፡፡ አሁን ይህንን ለመሥራት አቅደናል፡፡
ሪፖርተር፡- ይህ ማለት አንድ ኢንቨስተር ከውጭ እንደመጣ ከናንተ ጋር እንዲገናኝ ሆኖ፣ እናንተ የአዋጭነት ጥናት ሠርታችሁለት ብሎም ሌሎችን ሥራዎች ሠርታችሁለት ወደ ኢንቨስትመንት እንዲገባ ማስቻል ማለት ነው?
ወ/ሮ ፋንታዬ፡- እኛ አሁን ወደዛ ነው እየሄድን ያለነው፡፡ አሁን በዋነኛነት ፕሮግራሞችን እናዘጋጃለን፡፡ የአዋጭነት (የፊዚቢሊቲ) ሥራዎችን እንደምንሠራ ሆነን ነው የተቋቋምነው፡፡ ዋፋ ሦስት ዳይሬክተር ነው ያለው፡፡ አንደኛው ብራንድና ማስታወቂያ ነው፡፡ ሁለተኛ አስተዳደርና ፋይናንስ ነው፡፡ ሦስተኛው ኢንተርናሽናል ኢቨንት ነው፡፡ በኢንተርናሽናል ኢቨንት ውስጥ ኢንቨስተር ሪሌሽንና ፕሮሞሽን የሚባል አለን፡፡ ይህንን ሥራ እንድንሠራ ከመጀመርያ ጀምሮ ነው የተቋቋምነው፡፡
ሪፖርተር፡- ብዙ ዓይነት ኢንቨስትመንት አለ፡፡ ግብርና፣ ማይኒንግ፣ ማኒፋክቸሪንግ ተጠቃሾች ናቸው፡፡ ዋፋ እነዚህን የተለያዩ ዘርፎች የአዋጭነት ጥናት ሊሠራ የሚያስችል አቅም አለው?
ወ/ሮ ፋንታዬ፡- የምንሠራው ዋናው ሥራችን ይኼ ይሆናል፡፡ ሁለተኛ ሥራ በጋራ ይሠራል፡፡ ሁሉንም ባለሙያ አትቀጥረውም፡፡ አውት ሶርስ ታደርጋለህ፡፡ በማዕከል ደረጃ የተወሰነ ብቃት ያለው ባለሙያ ይዘህ ለሌሎቹ ሥራውን ትሰጣለህ፡፡
Read more...