የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር እዮብ ተካልኝ፥ በጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ወቅታዊ የአገሪቱ ምጣኔ ኃብታዊ ጉዳዮች በተመለከተ ለጋዜጠኞች መግለጫ ሰጥተዋል።
በመግለጫቸውም መንግሥት ለዘርፉ በሰጠው ትኩረትና ከነባራዊ ሁኔታ ጋር የተገናዘበ የትክክለኛ የፖለሲ ማሻሻያ በማድረጉ አበረታች ውጤት ማስመዝገብ ተችሏል ብለዋል።
የፖሊሲ ማሻሻያዎቹም የማይክሮ ኢኮኖሚ መረጋጋት ለማምጣት በሚያስችሉና የአገሪቱ ምጣኔ ኃብታዊ እድገት ቀጣይነት እንዲኖረው ትኩረት ያደረጉ መሆናቸውን ጠቁመዋል።
የተገኙትም ውጤቶች አገሪቱ የኮሮናቫይረስ ወረርሺኝ ጨምሮ ሌሎች ተፈጥሮዊና ሰው ሰራሽ ችግሮችን ተቋቁሞ የተገኘ መሆኑን ገልጸው ቀጣይነት ያለው ነው ብለዋል።
በዚህም በግብርናው ዘርፍ ዓመታዊ እድገቱ 5 ነጥብ 5 በመቶ ማድግ እንደቻለና በተለይም በበጋ ወቅት የመስኖ ሥራ የ220 በመቶ እድገት ማስመዝገቡን ጠቅሰዋል።
የማዕድን ዘርፍ በተለይም የወርቅ የውጭ ንግድ እድገትም 23 በመቶ ሆኖ መመዝገቡን ጠቁመዋል።
በፋይናስ ዘርፉም እድገት መመዝገቡን ጠቁመው የልማት ባንክና የንግድ ባንክ ትርፍ 22 በመቶ እንዲሁም የኢንሹራንስ ኩባንያዎች ትርፍ 16 በመቶ ማደጉን ተናግረዋል።
በተመሳሳይ የተቀማጭ ገንዘብ 13 በመቶ እንዲሁም ብድር ምጣኔ አቅርቦት በመቶ ማደጉን ገልጸዋል።
የውጭ ንግድ በዘንድሮ ዓመት 3 ነጥብ 6 ቢሊየን ዶላር በማስመዝገብ ከባለፈው ዓመት 19 በመቶ ብልጫ ማስመዘግቡን ተናግረዋል።
በዘንድሮው ዓመት ብቻ ከዚህ ቀደም ከነበረው ዓመታዊ ገቢ ላይ 600 ሚሊየን ዶላር ጭማሪ መገኘቱን ጠቅሰው ይህም ትልቅ ስኬት ነው ማለታቸውን ኢዜአ ዘግቧል።